ዘዳግም 32:30-49 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

30. መጠጊያ ዐለታቸው ካልሸጣቸው፣ እግዚአብሔር (ያህዌ) ካልተዋቸው በቀር፣አንድ ሰው እንዴት ሺሁን ያሳድዳል?ሁለቱስ እንዴት ዐሥር ሺሁን እንዲሸሹ ያደርጋሉ?

31. የእነርሱ መጠጊያ ዐለት እንደ እኛ መጠጊያዐለት አይደለምና፤ ጠላቶቻችንም እንኳ ይህን አይክዱም።

32. ወይናቸው ከሰዶም ወይን፣ከገሞራም እርሻ ይመጣል፤የወይናቸው ፍሬ በመርዝ፣ዘለላቸውም በምሬት የተሞላ ነው።

33. ወይናቸው የእባብ መርዝ፣የመራዥ እባብም መርዝ ነው።

34. “ይህ በእኔ ዘንድ ተጠብቆ ያለ፣በመዝገቤስ የታተመ አይደለምን?

35. በቀል የእኔ ነው፤ እኔ ብድራትን እመልሳለሁ፤ጊዜው ሲደርስ እግራቸው ይሰናከላል፤የመጥፊያቸው ቀን ቀርቦአል፤የሚመጣባቸውም ፍርድ ፈጥኖባቸዋል።”

36. ኀይላቸው መድከሙን፣ባሪያም ሆነ ነጻ ሰው አለመቅረቱን በሚያይበት ጊዜ፣ እግዚአብሔር (ያህዌ) ለሕዝቡ ይፈርዳል፤ለአገልጋዮቹም ይራራል።

37. እንዲህም ይላል፤ “መጠጊያ ዐለት የሆኗቸው፣እነዚያ አማልክታቸው የት አሉ?

38. የመሥዋዕታቸውን ስብ የበሉ፣የመጠጥ ቊርባናቸውንም የወይን ጠጅ የጠጡ አማልክት ወዴት ናቸው?እስቲ ይነሡና ይርዷችሁ!እስቲ መጠለያ ይስጧችሁ!

39. “እኔ ራሴ እርሱ እንደሆንሁ እዩ፤ከእኔም በቀር ሌላ አምላክ የለም፤እገድላለሁ፤ አድናለሁም፤አቈስላለሁ፤ እፈውሳለሁም፤ከእጄም የሚያስጥል ማንም የለም።

40. እጄን ወደ ሰማይ አነሣለሁ፤ለዘላለምም ሕያው እንደሆንሁ እናገራለሁ፤

41. የሚያብረቀርቅ ሰይፌን ስዬ፣እጄ ለፍርድ ስትይዘው፣ባላጋራዎቼን እበቀላቸዋለሁ፤የሚጠሉኝንም እንደ ሥራቸው እከፍላቸዋለሁ።

42. ሰይፌ ሥጋ በሚበላበት ጊዜ፣ፍላጾቼ በደም እንዲሰክሩ አደርጋለሁ፤ደሙ የታረዱትና የምርኮኞች፣የጠላት አለቆችም ራስ ደም ነው።”

43. አሕዛብ ሆይ፤ ከሕዝቡ ጋር ደስ ይበላችሁ፤እርሱ የአገልጋዮቹን ደም ይመልሳል፤ጠላቶቹንም ይበቀላል።ምድሪቱንና ሕዝቡን ይቤዣቸዋልና።

44. ሙሴም ከነዌ ልጅ ከኢያሱ ጋር መጥቶ የዚህን መዝሙር ቃሎች በሕዝቡ ጆሮ ተናገረ።

45. ሙሴም እነዚህን ቃሎች ሁሉ ለመላው እስራኤል ተናግሮ ከጨረሰ በኋላ፣

46. እንዲህ አላቸው፤ የዚህን ሕግ ቃሎች ሁሉ በጥንቃቄ ይጠብቁ ዘንድ ልጆቻችሁን እንድታዟቸው፣ እኔ ዛሬ በግልጥ የምነግራችሁን ቃሎች ሁሉ በልባችሁ አኑሩ።

47. ቃሎቹ ለእናንተ ሕይወታችሁ እንጂ እንዲሁ ባዶ ቃሎች አይደሉም፤ በእነርሱ ዮርዳኖስን ተሻግራችሁ፤ በምትወር ሷትም ምድር ረጅም ዘመን ትኖራላችሁ።

48. በዚያችም ዕለት እግዚአብሔር (ያህዌ) ሙሴን እንዲህ አለው፤

49. ከኢያሪኮ ማዶ ባለው የሞዓብ ምድር፣ ከዓባሪም ተራሮች አንዱ ወደ ሆነው ወደ ናባው ተራራ ወጥተህ ለእስራኤላውያን ርስት አድርጌ የምሰጣትን የከነዓንን ምድር አሻግረህ ተመልከት።

ዘዳግም 32