9. ጲላጦስም፣ “የአይሁድን ንጉሥ እንድፈታላችሁ ትፈልጋላችሁን?” ሲል ጠየቃቸው፤
10. ምክንያቱም የካህናት አለቆች ኢየሱስን አሳልፈው የሰጡት በቅናት መሆኑን ያውቅ ነበር።
11. የካህናት አለቆች ግን በርባንን በእርሱ ምትክ እንዲፈታላቸው እንዲጠይቁ ሕዝቡን አነሣሡ።
12. ጲላጦስም እንደ ገና፣ “እንግዲያው የአይሁድ ንጉሥ የምትሉትን ምን እንዳደርገው ትፈልጋላችሁ?” አላቸው።
13. እነርሱም እንደ ገና፣ “ስቀለው!” እያሉ ጮኹ።
14. ጲላጦስም፣ “ለምን? ምን የፈጸመው ወንጀል አለ” አላቸው።እነርሱ ግን፣ “ስቀለው!” እያሉ የባሰ ጮኹ።
15. ጲላጦስም ሕዝቡን ደስ ለማሰኘት ሲል በርባንን ፈታላቸው፤ ኢየሱስን ግን ገርፎ እንዲሰቀል አሳልፎ ሰጠው።
16. ወታደሮቹ ፕራይቶሪዮን ወደተባለ ወደ ገዡ ግቢ ወሰዱት፤ ሰራዊቱንም ሁሉ በአንድነት ሰበሰቡ።
17. ቀይ ልብስም አለበሱት፤ የእሾኽ አክሊል ጐንጒነው በራሱ ላይ ደፉበት።
18. ከዚያም፣ “የአይሁድ ንጉሥ ሆይ፤ ሰላም ለአንተ ይሁን!” እያሉ እጅ ነሡት፤
19. ራሱንም በበትር መቱት፤ ተፉበትም፤ ተንበርክከውም ሰገዱለት።
20. ካፌዙበት በኋላም ቀዩን ልብስ ገፈፉት፤ የገዛ ልብሱን አለበሱት፤ ሊሰቅሉትም ወሰዱት።
21. የአሌክሳንድሮስና የሩፎስ አባት ስምዖን የተባለ አንድ የቀሬና ሰው ከገጠር ሲመጣ መስቀሉን እንዲሸከም አስገደዱት።
22. ከዚያም ኢየሱስን፣ ትርጒሙ “የራስ ቅል ስፍራ” ወደተባለ ወደ ጎልጎታ ወሰዱት።
23. ከከርቤ ጋር የተቀላቀለ የወይን ጠጅም ሰጡት፤ እርሱ ግን አልተቀበለም።
24. ከዚያም ሰቀሉት፤ እያንዳንዱም ምን እንደሚደርሰው ለማወቅ ዕጣ ተጣጥለው ልብሱን ተከፋፈሉ።
25. ሲሰቅሉትም ጊዜው ከጠዋቱ ሦስት ሰዓት ነበረ።
26. የክሱ ጽሑፍም፣ “የአይሁድ ንጉሥ” የሚል ነበር።
27. ከእርሱም ጋር ሁለት ወንበዴዎችን አንዱን በቀኙ አንዱን በግራው ሰቀሉ።