1 ነገሥት 9:16-25 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

16. የግብፅ ንጉሥ ፈርዖን ወጥቶ በጌዝር ላይ አደጋ ጥሎ ያዛት፤ አቃጠላትም፤ ነዋሪዎቿን ከነዓናውያንን ገድሎ ለልጁ ለሰሎሞን ሚስት መዳሪያ አድርጎ ሰጥቶአት ነበር፤

17. ሰሎሞንም ጌዝርን መልሶ ሠራት፤ እንዲሁም የታችኛውን ቤትሖሮንን፣

18. ባዕላትን፣ በይሁዳ ምድር በምድረ በዳው የምትገኘውን ተድሞርን ሠራ፤

19. ደግሞም ማናቸውንም በኢየሩሳሌም፣ በሊባኖስና በሌሎች ግዛቶቹ ሁሉ ለመሥራት የፈለገውን፣ ሥንቅ የሚከማችባቸውን፣ ሠረገሎች የሚጠበቁባቸውን እንዲሁም ፈረሰኞች የሚቀመጡባቸውን ከተሞችና መንደሮች ሁሉ ሠራ።

20. ከእስራኤል ሕዝብ ያልሆኑትን ከአሞራውያን፣ ከኬጢያውያን፣ ከፌርዛውያን፣ ከኤውያውንና ከኢያቡሳውያን ሕዝቦች ሁሉ የተረፉትን፣

21. እስራኤላውያን ዘሮቻቸውን ለማጥፋት ያልቻሉትንና በምድሪቱ የቀሩትን እነዚህን እስከ ዛሬ እንደሚደረገው ሁሉ፣ ሰሎሞን ለግዳጅ ሥራ መለመላቸው።

22. ይሁን እንጂ ሰሎሞን ከእስራኤላውያን ማንንም ባሪያ አላደረገም፤ እነርሱ ወታደሮቹ፣ ሹማምቱ፣ የጦር አለቆቹ፣ ሻምበሎቹ፣ ባልደራሶቹ ነበሩ።

23. እነዚህም ሰሎሞን የሚያሠራውን የሕንጻ ሥራ የሚያከናውኑትን ሠራተኞች የሚቈጣጠሩ ናቸው፤ ቍጥራቸውም አምስት መቶ አምሳ ነበር።

24. የፈርዖን ልጅ ከዳዊት ከተማ ሰሎሞን ወዳሠራላት ቤተ መንግሥት ከመጣች በኋላ ሰሎሞን ሚሎንን ሠራ።

25. ሰሎሞንም ለእግዚአብሔር ባሠራው መሠዊያ ላይ በዓመት ሦስት ጊዜ የሚቃጠል መሥዋዕትና የኅብረት መሥዋዕት በማቅረብ፣ ከዚሁ ጋር በእግዚአብሔር ፊት ዕጣን ያሳርግ ነበር፤ በዚህ ሁኔታም የቤተ መቅደሱን ግዳጅ ተወጣ።

1 ነገሥት 9